MWAO_V2No9_አርብ ጥር ፳፫ ቀን ፪ሺህ፮ ዓም_(Fri 31 Jan 2014)_ውድ ኢትዮጵያውያን-ለዳር ድንበራችን ዘብ እንቁም … read in….PDF
ውድ ኢትዮጵያውያን፣ ለዳር ድንበራችን ዘብ እንቁም! አገራችን ኢትዮጵያ፣ እንኳን ሠፊ የግዛቷን አካል ቀርቶ፣ ብናኝ አፈሯ በውጪ ሰዎች መጫማያ ወደ ሌላ አገር እንዳይሄድ የሚከላከሉ መሪዎች እንደነበሯት ይታወቃል። ባዕዳን አፈሯን በጫማቸው እንዳይወስዱ ቀይ ባሕር ዳርቻ ላይ ጫማቸውን ያሳጠቡ የጀግኖች እናት ነበረች። ከአልማዟ፣ ከወርቋ እና ከከበሩ ድንጋዮቿ በማያንስ ሁኔታ ጥርኝ አፈሯን የሚወዱ መሪዎች እንደነበሯት የረጅም ጊዜ የነፃነት ተጋድሎዋ ታሪክ ሕያዉ ምስክር ነዉ። ኢትዮጵያ በአፍሪቃ አኅጉር የነፃነት ምሳሌ፣ የነፃነት ታጋዮች የመንፈስ ቀንዲል በመሆን ያገለገለችውም፥ ለአገሪቱ ነፃነት፣ ለሕዝቡ ሉዐላዊነት ብቻ ሳይሆን፣ ለጭብጥ አፈሯ ቀናዒ የሆኑ መሪዎች ስለነበሯት ነው። ጀግኖች በየጎራው ሆነው ካልጠበቁት አገር እንደሰው ተጓዥ መሆኑን አውቀው፣ ሕዝቡ የአገሩን ጠላት ነቅቶ እንዲጠብቅ ያላሰለሰ ጥረት የሚያደርጉ የንቁ መሪዎች ባለቤት በነበረችበት ወቅት፣ ኢትዮጵያ ታፍራ እና ተከብራ መኖሯ ይታወቃል። ተላላ ነው፡ አገር ተላላ ነው፣ ይጓዛል፡ ይሄዳል እንደሰው፣ በየበሩ ቁሞ ጀግና ካልመለሰው።